የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ አስፈጻሚዎችን ዝርዝር በመውሰድ የገለልተኝነት ማጣራት እንዲያከናውኑ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጥሪ አቀረበ

መጋቢት 2/2013 (ዋልታ) – የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ አስፈጻሚዎችን ዝርዝር በመውሰድ የገለልተኝነት ማጣራት እንዲያከናውኑ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጥሪ አቅርቧል፡፡

ቦርዱ በተለያየ መልኩ የመለመላቸው እና የመራጮች ምዝገባ ተግባር ላይ ሊሳተፉ የሚችሉ አስፈጻሚዎችን ዝርዝር ማዘጋጀቱን ገልጿል።

ፓርቲዎች ከቦርዱ የተሰጣቸውን ፍላሽ ይዘው ከፖለቲካ ፓርቲዎች የስራ ክፍል በመቅረብ የምርጫ አስፈጻሚዎቹን ዝርዝር መውሰድ የሚችሉ መሆኑን ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ፓርቲዎች አስተያየታቸውን የመራጮች ምዝገባ ከሚጀመርበት ቀን አስቀድሞ (እስከ መጋቢት 15) ለቦርዱ እንዲያቀርቡ ጠይቋል።

ከዚህ በፊትም በተለያዩ ዙሮች የምርጫ አስፈጻሚዎችን ዝርዝር ለፖለቲካ ፓርቲዎች ማቅረቡን ቦርዱ አስታውሷል፡፡